የአድዋ ድል የጥቁር ህዝቦች ሁሉ የነፃነት አርማ እና የኢትዮጵያውያን የአንድነት ምልክት መሆኑን በሚዘክር በዚህ መርሃ ግብር ላይ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ አባት አርበኞች፣ ምሁራን፣ ሰራተኞችና ተማሪዎች ተገኝተዋል። የበዓሉን የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝዳንት ሲሳይ ሙላቴ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ አድዋ ኢትዮጵያውያን መሪና ህዝብ፣ ወንድና ሴት ሳይለዩ በአንድነት ቆመው ለአለም ጥቁር ህዝቦች የነፃነት ብርሃን የፈነጠቁበት ታሪካዊ ክስተት ነው። ዶክተር ሲሳይ "አድዋ የጀግንነት ሀውልት ብቻ ሳይሆን፣ የኢትዮጵያዊያን የጥበብና የስትራቴጂ ውጤት ነው" በማለት ገልጸው፤ ዳግማዊ አፄ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ (ብርሃነ ዘኢትዮጵያ) ህዝብን ከመሪው በማቀናጀት የማይቻል የሚመስለውን ድል በተግባር ማሳየታቸውን አስገንዝበዋል። አክለውም የዛሬው ትውልድ ከአባቶቹ ጀግንነት ባለፈ በወቅቱ የነበረውን የጥበብና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም መማር እንዳለበትና በምርምር የታገዘ የቴክኖሎጂ ሽግግር በማምጣት አገራችንን ማሳደግ እንዳለብን አሳስበዋል። የዩኒቨርሲቲው የአፄ ዘርዓ ያዕቆብ የባህል፣ የታሪክና የቋንቋ ልማት ማዕከል ዳይሬክተር ዘመነወርቅ ዮሐንስ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዓሉ በመሪ ቃሉ መከበሩ ለታሪካዊው ድል የሚገባ እውቅና መሆኑን ገልጸዋል። ዳይሬክተሩ አክለውም "አድዋ ዘመን ተሻጋሪ ቅርስና ለትውልድ የሚቀጥል አሻራ ነው" በማለት፤ ድሉ ባለፈ ታሪክ ብቻ የሚወሰን ሳይሆን ለዛሬውም ሆነ ለሚቀጥለው ትውልድ የሚተርፍ "አሻራ ተረካቢ ውርስና ቅርስ" መሆኑን በአጽንኦት ገልጸዋል። ማዕከሉ በዓሉን ሲያዘጋጅ ታሪኩ በሰዎች አእምሮ ውስጥ ህያው ሆኖ እንዲጠበቅና ወጣቱ የአባቶቹን የጽናት ታሪክ ተረክቦ ለሀገሩ የሚጠበቅበትን አሻራ እንዲያኖር ለማስቻል መሆኑንም አስገንዝበዋል። ከዚህ የጥበብና የስትራቴጂ ዳራ በመነሳት፣ "የአድዋና የፓን አፍሪካዊነት እሴቶች ለእውነተኛ የአፍሪካ ነፃነት ማረጋገጫ መንገዶች" በሚል ርዕስ በዶ/ር አያሌው ዘለቀ ጥናታዊ ጽሁፍ የቀረበ ሲሆን፤ በተነሳው ሃሳብ ላይም ከተሳታፊዎች ጋር ሰፊ ውይይት ተካሂዷል። ዶ/ር አያሌው በጥናታቸው የአድዋ ድል ለፓን አፍሪካዊነት እንቅስቃሴ መንፈሳዊ ስንቅ መሆኑን ጠቅሰው፣ የኩዋሜ ንክሩማህን ራዕይና የቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴን አህጉራዊ ጥረት ከአድዋ ድል ጋር በማያያዝ አብራርተዋል። በቀረበው ጥናትና በተደረገው ውይይትም፤ የአፍሪካ የትምህርት ስርአት መፈተሽ፣ ድሉ በትምህርት ስርአቱ መካተቱን ማረጋገጥና ኢትዮጵያ በመሪነት ሚናዋ እንድትቀጥል ማስቻል የሚሉ ጠንካራ ምክረ-ሀሳቦች ተንፀባርቀዋል። ጥናቱ በመደምደሚያው አፍሪካ ዛሬም ድረስ በኒዮ-ሊበራሊዝም (አዲስ ቅኝ አገዛዝ) ስር መሆኗን በመረዳት፣ ድሉን እንደ ጽንሰ-ሀሳብና ፍልስፍና በመውሰድ ለጋራ አህጉራዊ ብልጽግና መጠቀም እንደሚገባ አመላክቷል። "ወጣቱ ከአድዋ አባቶቹ ብዙ የሚማረው ነገር ይኖራል" የሚለው የዚህ ትውልድ ዋነኛ የቤት ስራ መሆኑ የተመላከተበት ይህ በዓል፤ በልዩ ልዩ ስነ-ግጥሞች፣ የስእል ስራዎች፣ ዝክረ አድዋ ተውኔትና ታሪካዊ ትርኢቶች ታጅቦ በድምቀት ተጠናቋል።